"ጠንካራ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ክብካቤ ሥርዓቶችን ለመገንባት ዲጂታል ጤናን ጥቅም ላይ ማዋል" በሚል መሪ ሃሳብ ሶስተኛው የምስራቅ እና ደቡብ አፍሪካ ሃገራት የጤና መሪዎች የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ
ሦስተኛው ዓመታዊ አውደ ጥናት፤ በምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ከፍተኛ የጤና፣ የገንዘብ እና የኢንፎርሜሽንና የኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT) ባለሥልጣናትን በመሰብሰብ አገራዊ ትብብርን ለማጠናከርና የጋራ የመማማሪያ መረብ ለመፍጠር ያለመ ነው።
የአውደ ጥናቱ ዋና ዓላማ ይበልጥ ፍትሃዊ፣ ጠንካራ እና በበጀት ረገድ ዘላቂነት ያለው የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ሥርዓት ለመገንባት የሚያስችል የጋራ ቀጠናዊ የዲጂታል ጤና ራዕይን ማምጣት መሆኑን ያስረዱት የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ ናቸው።
ተሳታፊዎቹ በየአገራቱ ያለውን ተሞክሮ፣ የአፈጻጸም ማነቆዎችን እና የዲጂታል ጤና መፍትሔዎችን በሰፊው ተግባራዊ ለማድረግ የተገኙ ትምህርቶችን ይለዋወጣሉ፤ እንዲሁም ቴክኖሎጂ የጤና የሰው ኃይል አስተዳደርን እና የመረጃ ውህደትን እንዴት እንደሚያሳድግ ያላቸውን ቴክኒካዊ ግንዛቤ ያሳድጋሉ ሲሉ ሚኒስትሯ ተናግረዋል።