በጅግጅጋ ከተማ በተካሄደው 23ኛ የጤናው ዘርፍ ጉባኤ ተሳታፊ የነበሩ ሁሉም ታዳሚዎች የኮቪድ 19 ምርመራ እንደተደረገላቸው ተገለጸ።

  • Time to read less than 1 minute
RDT test

ይህም በርካታ ቁጥር ያለው ተሳታፊ ለሚገኝባቸው ወሳኝ  ሀገራዊ ሁነቶች  ምሳሌ የሚሆን ተግባር መሆኑ ተነግሯል። 
"ፈጣን ምላሽ ሰጪ የጤና ስርአት በአዲስ ምእራፍ" በሚል መሪ ቃል  የሱማሌ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት መዲና በሆነችው ጅግጅጋ  ሲካሄድ የሰነበተው የጤናው ዘርፍ ጉባኤ ሁሉም ተሳታፊዎች ከጉባኤው  አንድ ቀን አስቀድሞ የኮቪድ 19 ምርመራ የወሰዱበትና ከቫይረሱ ነጻ መሆናቸው የተረጋገጠ ተሳታፊዎች የተገኙበት እንዲሁም ሌሎችም  ሁሉም የጥንቃቄ መንገዶች የተተገበሩበት እንደሆነ ገልጸው  ለሌሎች ተመሳሳይ ሀገራዊ ሁነቶች ትምህርት የሰጠ እንደነበር ተሳታፊዎች ተናግረዋል። 

የጤና ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር  ዶክተር ተገኔ ረጋሳ ይህንን አስመልክተው እንደተናገሩትም 
ተሳታፊዎች ወደ ጅግጅጋ ከመጓዛቸው አስቀድሞ በጤና ሚኒስቴር ቅጥር ግቢ የምርመራ ማእከል መደራጀቱን እና ተሳታፊዎች የምርመራ አገልግሎት ማግኘታቸውን ወደ ማእከል መምጣት ላልቻሉት  ደግሞ በጉባኤው ስፍራ ፈጣን ምርመራ መደራጀቱን እና ለሁሉም ተሳታፊ አገልግሎት መስጠት መቻሉን አስረድተዋል። ይህም በጉባኤው ተሳትፎ ምክንያት የኮቪድ 19 እንዳይስፋፋ ከማገዙም በላይ ለሌሎች መሰል ብዙ ታዳሚ ለሚገኙባቸው አስፈላጊ ጉባኤዎች ትምህርት የሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። ሌሎች ሴክተሮችም ይህንን ተግባራዊ ቢያደርጉ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ያነሱት ዳይሬክተሩ ጤና ሚኒስቴርና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት  የኮቪድ 19 ፈጣን ምርመራ አገልግሎት   በነጻ እንዲያገኙ ያደርጋሉ ብለዋል።