የአፍሪካ ሲዲሲ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ዢን ካሴያ የጤና ሚኒስትር ዶ/ር ሊያ ታደሰ ላደረጉላቸው መልካም አቀባበል አመስግነው የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል ሲወስድ የነበራቸዉን እርምጃዎችን እንደሚያደንቁ ዶ/ር ዣን ገልጸዋል።
በተለይም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወረርሽኙ በተከሰተበት ወቅት ለብዙ የአፍሪካ ሀገራት ህይወት አድን የሆኑ የጤና ቁሳቁሶችን በማድረስ ያበረከተውን እስተዋጾ እንደሚያደንቁና የኢትዮዺያ ህብረተሰብ ጤና ኢኒሰቲትዩት የሀገሪቱን የጤና ስርዓት ለማሻሻል እየተጫወተ ያለውን ሚና አድንቀው ተናግረዋል። ዶ/ር ዣን ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ ያላትን ልምድና የሰው ሀይል ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት እንድታካፍልም ጠይቀዋል።
ጤና ሚኒስቴር ከአፍሪካ ሲዲሲ ጋር በተለያዪ የህብረተሰብ ጤና ጉዳዮች፣ ክትባትን ተደራሽ በማድረግና ለማምረት በሚደረገዉ ጥረት ዙሪያና በአጠቃላይ የጤና ስርአት በማጠናከር ዙራያ ያለዉ ትብብር ጠንካራ መሆኑንና በቀጣይም ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰራ ዶ/ር ሊያ ገልጸው፤ ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የሰው ሀብቷን ለማልማት ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ማፍሰሷን ያስታወሱት ዶ/ር ሊያ፤ ኢትዮጵያ ልምዷን ከማካፈል ባለፈ ያፈራችውን የጤናው ዘርፍ የሰው ሀብት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ለማካፈልም ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።
በውይይቱም ላይ ዶ/ር ሊያ እንደተናገሩት ኢትዮጵያ ከአለም ባንክ እና አለም አቀፍ ለጋሽ ድርጅቶች እንዲሁም ከአፍሪካ ሲዲሲ ጋር በመተባበር ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የአህጉሪቱ ሀገራትም የሚጠቅም የክትባት ማምረቻ ለማቋቋም እየሰራች ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ጤና ሚኒቴር ከአፍሪካ ሲዲሲ ዋና ዳይሬክተር ጋር በጠንካራ ትብብር ለመስራት ዝግጁ መሆኑን ዶ/ር ሊያ ተናግረዋል።